Thursday, July 12, 2012

በመጀመሪያ ቃል - ሎጎስ ነበር፣ በመጨረሻም እርሱ ነው!

“ከእናንተ ግንብ ሊሠራ የሚወድ ለመደምደሚያ የሚበቃ ያለው እንደሆን አስቀድሞ ተቀምጦ ኪሳራውን የማይቆጥር ማነው?? ያለዚያ መሠረቱን ቢመሠርት ሊደመድመውም ቢያቅተው፣ ያዩት ሁሉ፡- ይህ ሰው ሊሠራ ጀምሮ ሊደመድመው አቃተው ብለው ሊዘባበቱበት ይጀምራሉ።” (ሉቃስ 14፡28-30)

የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የነበረው ዮሃንስ፣ የወንጌሉን መልእክት መጻፍ በጀመረባቸው ጥቂት ዓረፍተ ነገሮች መካከል፣ ክርስቶስን በተመለከተ በዘመናት መካከል ላለው ግራ መጋባት ምክንያት የሆነና፣ ክርስቲያኖች - (ከእግዚአብሔር ዳግመኛ የተወለዱና ሁሉን የሚመረምሩበትና የሚረዱበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔር መንፈስ የተቀበሉ የእግዚአብሔር ልጆች) ትኩረት ሰጥተውና ጊዜ ወስደው ሊያጠኑትና ሊረዱት የሚገባ አንድ ቃል አለ። ይኸውም በአማርኛችን “ቃል” ተብሎ የተተረጎመው የግሪኩ “ሎጎስ” ነው። በእርግጥ ይሄ “ሎጎስ” የሚለው የግሪክ ቃል ከክርስትናም ውጪ፣ በፍልስፍናው ዓለም ከክርስቶስ ልደት በፊት ይኖሩ የነበሩና እነ አሪስጦትልን የመሳሰሉ የግሪክ ፈላስፎች የተለያዩ ጽንሰ ሃሳቦችን ለመዘርዘርና ለማስረዳት የሚጠቀሙበት ቃል ነበር። የእኔ አነሳስ ይሄንን ጠንካራ የግሪክ ቃል በዝርዝርና በጥልቀት ለመተንተን ሳይሆን፤ ነገር ግን ቃሉ የያዛቸውንና “የእግዚአብሔር ምሥጢር” የተባለውን ክርስቶስን ለማወቅ የሚያስችሉንን ጥቂት ጭብጦች ለማሳየት፣ እንዲሁም “እንደ ፍቃዱ ምክር ሁሉን የሚሰራ” የተባለለት አምላካችን እግዚአብሔር በልጁ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የጀመረውንና ይፈጽመው ዘንድ የሚተጋበትን ዘላለማዊ ሃሳብ በመጠኑም ቢሆን ለመረዳት የሚያስችሉንን ጥቂት የመንደርደሪያ ሃሳቦች ለማንሳት ነው።     

የፍጥረት ሁሉ ባለቤትና ፈጣሪ፤ የጥበብ፣ የእውቀትና የማስተዋል ሁሉ ምንጭ የሆነው አምላክ፣ እንደ ፍቃዱ ምክር ሁሉን የሚሠራው ልዑል…. የፍጥረትን መሠረት ከማስቀመጡ - ‘ኅልቆ መሳፍርት’ የሌለውን ፍጥረቱን ከመፍጠሩ በፊት አስቦአል፣ ዕቅድ ዘርግቶአል፣ ፕላን አውጥቶአል፣…. “አስቀድሞ ተቀምጦ ኪሳራውን ቆጥሮአል - He counted – calculated – computed the cost” ዓለማት ሳይፈጠሩ - ምንም ነገር ሳይኖር - “በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ዘንድ” የነበረው ሎጎስ፣ በ’ስትሮንግ’ የሒብሪውና የግሪክ መዝገበ ቃላት መሠረት የተተረጎመበትም አንዱ መንገድ ይኸው ነው። “ማሰብ፣ ማገናዘብ ወይም ምክንያቶችን ማስቀመጥ፣ ማስላት…” ሐዋርያው ጳውሎስ “በክርስቶስ ለማድረግ እንደወደደ እንደ አሳቡ….” በማለት ሲናገር፣ የእግዚአብሔር ኣሳብ ጅማሬ ክርስቶስ መሆኑን ለማሳየት ነው።

“በመጀመሪያ ቃል - ሎጎስ ነበር….” ዮሃ.1፡1

“እግዚአብሔር የመንገዱ መጀመሪያ አደረገኝ፣ በቀድሞው ሥራው መጀመሪያ። ከጥንቱ ከዘላለም ጀምሮ ተሾምሁ፣ ምድር ከመፈጠርዋ አስቀድሞ። ቀላያት ገና ሳይኖሩ እኔ ተወለድሁ፣ የውኃ ምንጮች ገና ሳይፈልቁ። ተራሮች ገና ሳይመሠረቱ፣ ከኮረብቶች በፊት እኔ ተወለድሁ፣ ምድሪቱንና ሜዳውን ገና ሳይፈጥር የመጀመሪያውንም የዓለም አፈር።” (ምሳ.8፡22-26)

እግዚአብሔር ማንም ሊያየው በማይችል ብርሐን ውስጥ የሚኖር፣ ከቅድስናው ክብር የተነሳ ምንም ‘ነገር’ በፊቱ ሊቆም የማይችል፣ ግርማው የሚያስፈራ አምላክ ነው። ሙሴ “እባክህ ክብርህን አሳየኝ” ብሎ በለመነው ጊዜ፣ “ሰው አይቶኝ አይድንምና ፊቴን ማየት አትችልም" ነበር ያለው። የእርሱን ባሕሪይና ማንነትስ ሊረዳው የሚችል ማነው?... ስለዚህ ይህ የማይታየው አምላክ ከሁሉ በፊት የሚታየውን ፍጥረት የሚፈጥርበትን፣ ለሚፈጥረው ፍጥረት ራሱን የሚገልጥበትን ወይም ከፍጥረቱ ጋር የሚገናኝበትን መንገድ ማዘጋጀት ነበረበት። አሁንም “ሎጎስ” የሚለው ቃል፤ የመለኮት መታየትና መገለጥን፣ አንድን አካል ወክሎ መናገርን፣ ከሁለተኛ ወገን ጋር የሚደረግ ግንኙነትን፣ መካከለኝነትን፣…. የሚያመለክት ቃል ነው። ዓለም ሳይፈጠር - ‘ምድር ከመፈጠርዋ አስቀድሞ፣ ቀላያት ገና ሳይኖሩ የውኃ ምንጮች ገና ሳይፈልቁ፣ ተራሮች ገና ሳይወለዱ …. እግዚአብሔር የመንገዱ መጀመሪያ ያደረገውና አስቀድሞ የወለደው “ሎጎስ”፣ ዓለማትን ሁሉ “በእርሱ” ከመፍጠሩና ከማጋጠሙም በላይ፣ ከፍጥረቱ ሁሉ ጋር የሚገናኝበት፣ ራሱንም ለፍጥረቱ የሚገልጥበትና የሚያስተዋውቅበት መልኩና ምሳሌው ነው።

ወንጌላዊው ዮሃንስ፤ እግዚአብሔር ሥራውን ሁሉን ያቀደበትንና ያዘጋጀበትን ‘ብሉ ፕሪንት’፣ የፈጠረበትንና ያጋጠመበትን ሕይወት፣ ደግሞም የማይታየውን ማንነቱን ለፍጥረቱ ሁሉ የገለጠበትን “መልክ” - በመጀመሪያ በእርሱ ዘንድ የነበረውን ሎጎስ “እግዚአብሔር ነበር” ማለቱን በዚህ መንገድ ስንረዳው ብቻ ነው፣ ሃይማኖት የፈጠረውን ሳይሆን በእግዚአብሔር ዘንድ ያለውን ክርስቶስን ማየት የሚሆንልን።   

“እርሱም የማይታይ አምላክ ምሳሌ ነው
፣ የሚታዩትና የማይታዩትም ዙፋናት ቢሆኑ ወይም አለቅነት ወይም ሥልጣናት፣ በሰማይና በምድር ያሉት ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋልና ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኩር ነው፣ ሁሉ በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሮአል፣ እርሱም ከሁሉ በፊት ነው፣ ሁሉም በእርሱ ተጋጥሞአል።” (ቆላ.1፡15-17)

“ሁሉ በእርሱ ሆነ፣ ከሆነውም አንዳች ነገር ያለእርሱ አልሆነም”  (ዮሃ.1፡3)

“እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ በተለያየ ጊዜና በልዩ ልዩ መንገድ በነቢያት ለአባቶቻችን ተናግሮ፣ በዚህ በመጨረሻ ዘመን ግን ሁሉን ወራሽ ባደረገውና ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ ለእኛ ተናገረን። እርሱ የእግዚአብሔር ክብር ነጸብራቅና የባሕሪዩ ትክክለኛ ምሳሌ ሆኖ በኃይል ቃሉ ሁሉን ደግፎ ይዞአል፤….” (ዕብ1፡1-3 አዲሱ መደበኛ ትርጉም)

እግዚአብሔር ፍጥረትን የፈጠረበትና የመሠረተበት፣ ያገናኘበትና ያዋቀረበት፣ እንዲሁም ደግፎ የያዘበት ሎጎስ - የመንገዱ መጀመሪያ ነበር። የማይታየው አምላክ የዘላለም መኖሪያው - የቤቱ መሠረት ያደረገውም “በእግዚአብሔር መልክ” ይኖር የነበረውንና፣ ነገር ግን የኃጢአታችንንና የበደላችንን ዋጋ ለመክፈል - ቤዛ ለመሆን፣ በቀደመው ክብሩና ማንነቱ ሳይሆን ራሱን ባዶ አድርጎና ፍጹም ሰው ሆኖ (ፍጹም ሰው የሆነበትም ዓላማ እርሱ ራሱ ተፈትኖ መከራን በመቀበል እኛን ሊረዳና ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ የታመነና የሚምር ሊቀ ካህን ለመሆን እንደሆነ ልብ ይሏል) ለ33 ½ ዓመታት በፕላኔታችን ላይ የተመላለሰውን ይሄንኑ አንድያ ልጁን ክርስቶስን ነው። ደግሞም በዘመናት ፍጻሜ ያደርገውና ይፈጽመው ዘንድ ከዘላለም ዘመናት በፊት ያቀደውና የወሰነው አሳቡም “በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።” (ኤፌ.1፡10)

የእግዚአብሔር ሥራ መሠረቱ፣ “የመንገዱ መጀመሪያ፣ ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኩር፣ በእግዚአብሔር ፍጥረት መጀመሪያ የነበረው - አልፋ ….. ክርስቶስ ነው። ፍጥረት ሁሉ የቆመበት መሠረት፣ የተደገፈበት ምሶሶ፣ የተዋቀረበት መዋቅር፣… ክርስቶስ ነው። የእግዚአብሔር ሥራ ፍጻሜ፣ መጨረሻውና ድምድማቱ - ዖሜጋ….. ክርስቶስ ነው። የሕይወታችንና የእምነታችን መሠረት፣ ሐዋርያና ሊቀ ካህን፣ ጀማሪና ፈጻሚ፣ የቆምንበት ሕያው ዓለት… የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በአዳም በደልና መተላለፍ ወድቀንና ከእርሱ ተለይተን የነበርነውን እኛን፣ አምላካችንና አባታችን የሆነው እግዚአብሔር፣ ከወደቅንበት ያነሳን
በክርስቶስ ነው። በእርሱ ዳግመኛ ወለደን፣ ቀድሞውንም የነበረው ሃሳቡ እኛን በመልኩ እንደምሳሌው መፍጠር ነበርና ወደዚያ መልኩና ምሳሌው - ወደ ክርስቶስ እያሳደገን ነው። “እንደ ፈቃዱ ምክር ሁሉን የሚሠራ” የተባለለት ልዑል እግዚአብሔር (Sovereign God)፤ ለክብሩ ምሥጋና ይሆን ዘንድ በክርስቶስ የጀመረውን ይህን መልካም ሥራ ይፈጽመው ዘንድ የታመነ ብቻ ሳይሆን፤ በጥበብ፣ በእውቀትና በማስተዋል  የተሞላ ብርቱ አምላክ ነው።     

No comments:

Post a Comment