Tuesday, November 20, 2012

የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ የሚገኝ አንድነት!!


“እንግዲህ በጌታ እስር የሆንሁ እኔ በተጠራችሁበት መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ፤ በትሕትና ሁሉና በየዋህነት በትዕግሥትም፤ እርስ በርሳችሁ በፍቅር ታገሡ፤ በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ። በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደ ተጠራችሁ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ፤ አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት፤ ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ።” (ኤፌ.4፡1-6)

“ለምንድነው ዛሬ ‘ክርስቲያኖች’ ተብለን በምንጠራው ወንድማማች የእግዚአብሔር ልጆች መካከል በቀድሞው ዘመን በሰናዖር ምድር እንደሆነው አይነት የቋንቋ መደበላለቅና ትርምስ የሆነው?” የሚለው ጥያቄ በአእምሮዬ ውስጥ መጮህ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል። “የክርስቲያኖች ሕብረትና አንድነት” የሚለው የውይይት መድረክም የተጀመረው ይሄን ጥያቄ በክርስቲያን ወንድሞቼም አእምሮ ውስጥ ለመጫርና፤ ለዚህ ግራ መጋባት፣ መበታተንና መከፋፈል ምክንያት የሆኑትን ነገሮች ሕያው በሆነው በእግዚአብሔር ቃል መሠረት ለመመርመርና ለመለየት፣ ከዚያም ከማይጠፋው ዘር የተወለዱት ነገር ግን ሐይማኖት በፈጠራቸው ልዩ ልዩ “ጎሳዎች” ተከፋፍለው ወዲያና ወዲህ የተበታተኑትን “የደረቁ አጥንቶች” እርስ በርሳቸው ለማቀራረብ ነበር። በእርግጥ ዛሬ ስንቶቹ ወንድሞቼ ይህን ጥያቄ እየጠየቁ እንደሆነ አላውቅም።

ከላይ ባነበብነውና የተወደደው ወንድማችን ጳውሎስ ለኤፌሶን ቅዱሳን በጻፈው መልእክቱ ውስጥ እንደገለጠው፤ አንድ ተስፋ፣ አንድ አካል፣ አንድ መንፈስ፣ አንድ ጌታ፣ አንድ እምነት፣ አንድ ጥምቀት እና ከሁሉ በላይ የሚሆን፣ በሁሉም የሚሠራ፣ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ። ይሄ አንድ አምላክ እና የሁሉም አባት የተባለው እግዚአብሔር ለሰዎች ሁሉ የሰጠው አንድ ተስፋ እርሱም የዘላለም ሕይወት ተስፋ ነው። ሰዎች ይህን የዘላለም ሕይወት ተስፋ የሚቀበሉት ደግሞ፤ እግዚአብሔር ለዓለም ሁሉ የኃጢአት ሥርየትና የሕይወት ምንጭ እንዲሆን የላከውን አንድያ ልጁን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን አምነው ሲቀበሉ ነው። ክርስትና የተባለው አንድ እምነት የተመሠረተው በዚህ ሕያው እውነት ላይ ነው። “አንድ ጌታ” የተባለው ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ማመን!!! እግዚአብሔር አንድ ጊዜ ከመሠረተው ከዚህ የእምነትና የሕይወት መሠረት በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልም። ዛሬ ኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክ፣ ፕሮቴስታንት፣ የይሖዋ ምስክር፣ “ኦንሊይ ጂሰስ”፣ አድቬንቲስት፣ ሙሉ ወንጌል፣ …. በሚሉና ሐይማኖት በፈጠራቸው የተለያዩ ቅጥሮች ውስጥ ሆነውና በተለያየ አስተምህሮ ተከፋፍለው በጎሪጥ የሚተያዩትን ወንድሞቼን አንድ ጥያቄ ልጠይቅ እወዳለሁ፡- የእምነታችሁና የሕይወታችሁ መሠረት ዬትኛው የእምነት መግለጫ ወይም አስተምህሮ ነው????????

ማንም ይህን ጥያቄ ከክርስቶስ ትምሕርትና ከሐዋርያቱ መልእክቶች ውጪ በሆኑ ሌሎች አስተምህሮዎች ለመመለስ ከሞከረ፣ እግዚአብሔር ከመሠረተው የእምነትና የሕይወት መሠረት ውጪ ራሱን ያገኛል። በመሆኑም “እኔ የክርስቶስ ደቀ መዝሙር - ክርስቲያን ነኝ” ለማለት ካለመቻሉም በላይ እግዚአብሔር የሰጠውን የዘላለም ሕይወት ተስፋ ለመቀበሉ እርግጠኛ ሊሆን አይችልም። የመጀመሪያዎቹ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት የነበሩት ሐዋርያት አስቀድመው ራሳቸውን በዚህ እግዚአብሔር በመሠረተው የእምነትና የዘላለም ሕይወት መሠረት ላይ ካቆሙ በኋላ ነው ለእኛ ይህንን አንድ የእምነትና የሕይወት መሠረት ያኖሩልን።
“ስምዖን ጴጥሮስ፡- ጌታ ሆይ ወደማን እንሄዳለን?? አንተ የዘላለም ሕይወት ቃል አለህ፤ እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ አምነናል፣ አውቀናልም ብሎ መለሰለት” (ዮሃ.6፡28-29)

የክርስቶስ ሐዋርያትም ሆኑ የእነሱን እግር ተከትለው ወንጌልን ለዓለም ሁሉ መስበክ የጀመሩት የመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የእግዚአብሔር መንግሥት ሠራተኞች፣ የሰዎችን እምነትና ሕይወት የመሠረቱት በዚህ በተፈተነው፣ በከበረውና መሠረቱም በጸናው ሕያው ዓለት - በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነበር። ሐዋርያቱ ወንጌልን ከኢየሩሳሌም ጀምረው በሰበኩበት በዚያ ዘመን በመጀመሪያው የሐዋርያት አገልግሎት ወደዘላለም ሕይወት ተስፋ ከተጠሩት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ተርታ የምናገኘው፣ ለእሥራኤል አምላክ ለመስገድ ወደ ኢሩሳሌም ሄዶ የነበረው ኢትዮጵያዊውን የመንግሥት ባለሟል ነው። ፊሊጶስ በቀጥታ ከእግዚአብሔር መንፈስ በተሰጠው ትዕዛዝ መሠረት ለዚህ ኢትዮጵያዊ የክርስቶስን የመስቀል ላይ ሕማም ከሚናገረው ከኢሳያስ መጽሐፍ ጀምሮ ስለኢየሱስ ወንጌልን ከሰበከለት በኋላ፣ ኢትዮጵያዊው በውኃ ተጠምቆ የክርስቶስ ደቀ መዝሙር ለመሆን ሲወስን ከፊሊጶስ የቀረበለት አንድ ቅድመ ሁኔታ ነበር፡- “በፍጹም ልብህ ብታምን ተፈቅዶልሃል!” ኢትዮጵያዊው የመለሰው መልስ፣ ወይም በአንደበቱ የተናገረው የእምነቱ መግለጫ ልክ ሐዋርያቱ አስቀድመው እምነታቸውንና ሕይወታቸወን የመሠረቱበት የእምነት መግለጫ ነበር፡- “ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ!!!”     

አሁንም ኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክ፣ ፕሮቴስታንት፣ የይሖዋ ምስክር፣ “ኦንሊይ ጂሰስ”፣ አድቬንቲስት፣ ሙሉ ወንጌል፣ …. በሚሉና ሐይማኖት በፈጠራቸው የተለያዩ ቅጥሮች ውስጥ ሆነውና በተለያየ አስተምህሮ ተከፋፍለው በጎሪጥ የሚተያዩትን ወንድሞቼን ደግሜ አንድ ሌላ ጥያቄ ልጠይቅ፡- ከእናንተ መካከል ክርስቶስና ጌታ የተባለው ኢየሱስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ፣ ደግሞም ይህ የእግዚአብሔር አንድያ ልጅ በመስቀሉ ላይ የከፈለውን ቤዛ፣ ሞቱንና ትንሣኤውን የማያምን ማነው??? በእርግጥ ልክ እንደሐዋርያቱና ከላይ እንዳየነው ኢትዮጵያዊ እምነታችሁ ከዚህ እግዚአብሔር ራሱ ከመሠረተው የእምነትና የሕይወት መሠረት ከጀመረ፣ አንዳችሁ ሌላኛችሁን “አንድ እምነት” ከተባለው ክርስትና ውጪ አድርጋችሁ እንድታዩ፣ ደግሞም እንድትከፋፈሉና እንድትከፋፉ፣ እንድትበታተኑና እንድትለያዩ አዚም ያደረገባችሁ ማነው???

“አንድ እምነት” የተባለው ክርስትና የሚጀምረው የእግዚአብሔርን ልጅ በማመን ነው። ይሄ እምነት ደግሞ መንፈስ ከሆነው እግዚአብሔር ይወልደናል። “ክርስቶስ ነው ብሎ በኢየሱስ የሚያምን ከእግዚአብሔር ተወልዶአል” የሚለውን ሐዋርያዊ ትምሕርት ያለምንም ቅድመ ሁኔታና ማመካኘት (Reasoning) እንቀበለው ዘንድ ግድ ነው። ከመንፈስ የተወለደ ደግሞ መንፈስ ነው። ክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ በማመን ዳግመኛ የተወለድነውም ሆነ በዚህ ዳግመኛ ልደት በአንድ ተስፋ ወደ አንድ አካል የተጠመቅነው በዚሁ በተወለድንበት አንዱ መንፈስ ነው። አንድ እምነት፣ አንድ ጥምቀት፣ አንድ አካል፣ አንድ መንፈስ፣ አንድ ጌታ፣ አንድ አምላክ የሁሉም አባት ነው ያለው። ታድያ የእምነታችንና የሕይወታችን መሠረት በሆነው ሕያው ዓለት - በአንዱ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ መቆማችንን፣ “የማይጠፋ” ከተባለው ከአንዱ ዘር መወለዳችንን፣ በአንድ የዘላለም ሕይወት ተስፋ መጠራታችንን፣ አንዱን መንፈስ ጠጥተን በአንዱ መንፈስ ወደ አንድ አካል መጠመቃችንን፣ በክርስቶስ ኢየሱስ ልናመልከው የተገባውም “አንድ አምላክ የሁሉም አባት” የተባለውን እግዚአብሔርን መሆኑን እንዳናይ ማን አዚም አደረግብን????

ኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክ፣ ፕሮቴስታንት፣ የይሖዋ ምስክር፣ “ኦንሊይ ጂሰስ”፣ አድቬንቲስት፣ ሙሉ ወንጌል…. መባባላችን ባይከፋም፣ እነዚህ ስሞች የመቀባበላችን ወይም የመለያየታችን ምክንያት መሆናቸው ግን በእጅጉ የሚያሳዝን ነው። ደግሞም እርስ በእርሳችን በክርስቶስ እንዳንተያይ ሐይማኖት በዓይናችን ፊት የሰፋቸው መጋረጃዎች፣ የገነባቸው ግንቦች ሆነው እርስ በእርሳችን ላንያያዝ ተከፋፍለን መቆማችን፣ አንዳችን በአንዳችን ላይ ጣታችንን እየቀሰርን፣ እያወገዝንና እየተሰዳደብን በቅናትና በክርክር እድሜአችንን መጨረሳችን፤ ያኔ በመጀመሪያው ክ/ዘመን እንደነበሩትና “አንተ የጳውሎስ፣ እኔ ደግሞ የአጵሎስ፣ እሷ ደግሞ የኬፋ….” እየተባባሉ እንደተለያዩት ሥጋውያኑ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች መሆናችንም አይደል??? ያኔስ እግዚአብሔር የላከው ጳውሎስ “ክርስቶስ ተከፍሎአልን?” በማለት በአንዲት ቃል መልሶ ሰበሰባቸው። ዛሬስ????


“እርሱም አንዳንዶቹ ሐዋርያት፣ ሌሎቹም ነቢያት፣ ሌሎቹም ወንጌልን ሰባኪዎች፣ ሌሎቹም እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ ሰጠ፤ ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት፣ ሙሉ ሰውም ወደመሆን፣ የክርስቶስም ሙላቱ ወደሚሆን ወደሙላቱ ልክ እስክንደርስ ድረስ፣ ቅዱሳን አገልግሎትን ለመሥራትና ለክርስቶስ አካል ሕንጻ ፍጹማን ይሆኑ ዘንድ።” (ኤፌ.4፡11-13)


               

Sunday, November 4, 2012

እግዚአብሔርን መምሰል - የመዳናችን ፍጻሜ!!!!!


ሰው “ዳነ” የሚባለው መቼ ነው??? ይህን ጥያቄ አጭርና ግልጽ በሆነ መንገድ ስንመልስ፣ ሰው “ዳነ” የሚባለው አስቀድሞ በእግዚአብሔር ወደተፈጠረበት መልክና ምሳሌ ሲመለስ ነው። ይሄ ደግሞ የቀናት ወይም የዓመታት ውጤት ሳይሆን በዘመናት መካከል በሚከናወን መንፈሳዊ ሂደት (Spiritual Process) የሚፈጸም የእግዚአብሔር ድንቅ ሃሳብ ነው። ይሄ ሃሳቡም እግዚአብሔር ለሰው ሁሉ!! እደግመዋለሁ፤ ለሰው ሁሉ ያለውና የማይለወጥ ብቻ ሳይሆን ሳይፈጸም የማይቀር ዘላለማዊ ሃሳቡ ነው። ይህንንም ሃሳቡን ነው ገና በማለዳ "ሰውን በመልካችን እንደምሳሌአችን እንፍጠር" በማለት የገለጠው። ምንም እንኳን የመጀመሪያው ሰው ምሉዕና ፍጹም በሆነ መልኩ ባይሆንም በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ እንደተፈጠረና፣ ነገር ግን በሰይጣን ተንኮል ተታልሎ ከዚህ መልክ እንደወደቀ መጽሐፍ ቢነግረንም ቅሉ፣ እግዚአብሔር ሰውን በመልኩ እንደምሳሌው የመፍጠርና የማግኘት ዓላማው በሰይጣን ሴራ ተበላሸ ወይም ከሸፈ ማለት አይደለም። ይልቁንም ተገለጠ እንጂ!!!!

እግዚአብሔር ዓለም ሳይፈጠር በክርስቶስ ባቀደው ዘላለማዊው ሃሳቡ መሠረት፣ በክርስቶስ ኢየሱስ ወንጌል ለዚህ የከበረ የእግዚአብሔር ዓላማ ቀድመው የተጠሩ (The called – out = Church)
ዛሬ በዚህ ሕይወት - በሥጋ ሳሉ በእግዚአብሔር ቅዱስ መንፈስና በጸጋው አሰራር ወደዚህ መልክና ምሳሌ ለመድረስ እየተሰሩና እየተዘጋጁ ነው። ከእነዚህ ኣማኞች መካከል በሥጋ ይኖሩ ዘንድ እግዚአብሔር በሰጣቸው ዘመን ፍጹም በሆነ መታዘዝ ወደዚህ የከበረ የእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የሚደርሱቱ “የእግዚአብሔር መንግስት ወራሾች” ወይም “በኩራት” ወይም “ድል ነሺዎች” ይባላሉ። እነዚህ ድል ነሺዎች ከአጠቃለዩ የሰው ልጆች ቁጥር አንጻር ብቻ ሳይሆን፣ በቤተክርስቲያን ካሉ አማኝ ወንድሞች መካከል ሲታዩ እጅግ በጣም ጥቂቶች ናቸው። ለዚህም ነው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ “ታናሽ መንጋ” ብሎ የጠራቸው።

“የክብር
አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እርሱን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ። ይህም የልባችሁ ዓይኖች ሲበሩ የመጥራቱ ተስፋ ምን እንዲሆን በቅዱሳንም ዘንድ ያለው የርስት ክብር ባለ ጠግነት ምን እንዲሆን ለምናምን ከሁሉ የሚበልጥ የኃይሉ ታላቅነት ምን እንዲሆን ታውቁ ዘንድ ነው” (ኤፌ.1፡17-19)

ዛሬ በዚህ ዘመን ከሚኖሩ የሰው ልጆች ሁሉ መካከል በክርስቶስ ወንጌል እንደተጠሩ የእግዚአብሔር ልጆች ሆነን ራሳችንን ስናይ፤ የተጠራነው የእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ ወደሆነው ወደ ክርስቶስ ፍጹም ሙላት ለመድረስ ነው። ርስታችንም እርሱ ነው። በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን መምሰል!!! መዳናችንም “ተፈጸመ!” የሚባለው እዚህጋ ስንደርስ ነው። በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን ስንመስል!!!!  እግዚአብሔር ማንን ይመስላል?? የማይታየው ባህሪው ደግሞም አምላክነቱ በተፈጠሩት ሁሉ ግልጥ ሆኖ እንደታየ መጽሐፍ ይመሰክራል። ወንድማችን ደረጀ ከበደ በመዝሙሩ እንደተቀኘው፡- የጠራው ሰማይ፣ በጠራው ሰማይ ላይም የተበተኑት የማይቆጠሩ ከዋክብት፣ የተራሮች ግርማ፣ የውቅያኖስ ስፋትና ጥልቀት... እነዚህና ሌሎች ሊቆጠሩ የማይችሉ የእግዚአብሔር  ፍጥረታት ሁሉ የእርሱን ጥበብ፣ እውቀትና ማስተዋል፣ ኃይልና ችሎታ፣ ቸርነትና ደግነት፣ ጽድቅና ቅድስና፣ ርህራሄና ፍቅር፣ ፍርድና ምሕረት፣ .... የሚሰብኩ መጻሕፍት ናቸው።

ነገር ግን የዕብራውያን ጸሐፊ እንደመሰከረው እግዚአብሔር የዘመናት ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ የክብሩ መንጸባረቅና የባህሪው ምሳሌ በሆነው አንድያ ልጁ በኩል ፍጹም ልዩ በሆነ መንገድ ራሱን ገልጦአል። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ “እኔን ያየ አብን አየ” በማለት የተናገረውም ለዚህ ነው። የእግዚአብሔር ዓላማም እነዚህን በክርስቶስ የተገለጡና የታዩትን ባህሪያቱን፤ ማለትም፡- ጥበቡን፣ እውቀትና ማስተዋሉን፣ ኃይልና ችሎታውን፣ ቸርነትና ደግነቱን፣ ጽድቅና ቅድስናውን፣ ርህራሄና ፍቅሩን፣ ፍርድና ምሕረቱን፣ ሰላሙን፣ በጎነቱን ... በሰው ሁሉ ውስጥ ማግኘት ነው። በዚህ ዘላለማዊ ሃሳቡም መሰረት፣ ዛሬ እኛ በምድር ከሚኖሩት አሕዛብ ሁሉ መካከል ይህን ባህሪውን ለመካፈል ብቻ ሳይሆን በሕይወት አካሄዳችንም በመግለጥ ለእግዚአብሔር ክብርን ለማምጣት ተለይተን ተጠርተናል። “የተጠሩ ብዙዎች የተመረጡ ግን ጥቂቶች ናቸው” ተብሎ እንደተጻፈው፤ መዳናችን ፍጹም ሆኖ ከታመኑትና ከተመረጡት ወገኖች መካከል መቆጠር የምንችለው ግን፣ ዛሬ በተጠራንበት መጠራት እንደሚገባ እየተመላለስን በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን ወደመምሰል ማደግ ከሆነልን ብቻ ነው።

“እንግዲህ አሕዛብ ደግሞ በአእምሮአቸው ከንቱነት እንደሚመላለሱ ከእንግዲህ ወዲህ እንዳትመላለሱ እላለሁ በጌታም ሆኜ እመሰክራለሁ። እነርሱ ባለማወቃቸው ጠንቅ በልባቸውም ደንዳንነት ጠንቅ ልቡናቸው ጨለመ፥ ከእግዚአብሔርም ሕይወት ራቁ፤ደንዝዘውም በመመኘት ርኵሰትን ሁሉ ለማድረግ ራሳቸውን ወደ ሴሰኝነት አሳልፈው ሰጡ። እናንተ ግን ክርስቶስን እንደዚህ አልተማራችሁም፤ በእርግጥ ሰምታችሁታልና፥ እውነትም በኢየሱስ እንዳለ በእርሱ ተምራችኋል፤ ፊተኛ ኑሮአችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ፥ በአእምሮአችሁም መንፈስ ታደሱ፤ ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ።” (ኤፌ.4፡17-24)

ይህን በክርስቶስ ኢየሱስ የሆነውንና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲስ ማንነት ፈጽመን መልበሳችን ነው የመዳናችን ዋስትና! ይሀም አዲስ ልብስ የመንግሥቱ ግብዣ እድምተኞች፣ የአዲሲቱ ኢየሩሳሌም “ዜጎች” ያደርገናል። እዚህጋ ካልደረስን ወይም ይህን አዲስ ልብስ ፈጽመን ካለበስን በቀር አፋችንን ሞልተን “ድነናል!” ማለት አንችልም። የመዳናችን ፍጻሜ እግዚአብሔርን መምሰል ነውና!!! እግዚአብሔር በሰጣቸው በዚህ ዘመን ይህን በክርስቶስ የሆነውን አዲስና የከበረ ማንነት ፈጽመው የለበሱ ክርስቲያኖች ድል ነስተዋልና “በሁለተኛው ሞት አይጎዱም!” ነገር ግን ደግሞ የተጠሩት ብዙዎች የታመኑት ግን ጥቂቶች እንደመሆናቸው መጠን፣ በዚህ ሕይወት ድል ያልነሱትና ያልታመኑት ብዙዎች ግን በውጭ ወዳለው ጨለማ መጣላቸው አይቀሬ ነው። ለምን ቢሉ አሮጌውን ልብስ ለብሶ የመንግሥቱ ግብዣ እድምተኞች፣ የቅድሰቲቱ ከተማ “ነዋሪዎች” መሆን ስለማይቻል!!! በውጭ ያለው ስቃይና መከራ፣ ሐዘኑና ጥርስ ማፋጨቱ፣ በዲን የሚቃጠለው እሳት….. የቅጣቱና የፍርዱ ኃይለኝነት የተገለጠባቸው መንገዶች ናቸው። በውጭ መጣልና በዚህ ሁኔታ ውስጥ መገኘት የእግዚአብሔር ቁጣና ፍርድ ነውና እጅግ አስፈሪ መሆኑ የማይካድ ነው። ከዚህም ፍርድ በታች ላለመገኘት አማራጩ በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ የራስን መዳን ለመፈጸም ክርስቶስ በሚሰጠን ኃይልና በጸጋው ጉልበት መጋደል ነው። የእግዚአብሔርን ጽድቅና ቅድስና፣ ይኸውም በክርስቶስ ያለውን መልኩና ምሳሌውን በፍርድና በቁጣው ከመካፈል ይልቅ፤ በጸጋው ትምህርትና በምሕረቱ ብዛት መካፈል ዛሬ ለእግዚአብሔር ልጆች ብቻ የተሰጠ
የእግዚአብሔር የአምላካችንና የአባታችን ውዴታና ቸርነት ነው።